በጉባዔው ም/ሰብሳቢ ክቡር አቶ ሠለሞን አረዳ የተመራው የሕገ መንግሥት ጉዳዮች አጣሪ ጉባዔ ልዑካን ቡድን ጀርመን በርሊን የልምድ ልውውጥ አካሄደ
February 14, 2020
ለመከላከያ ኮንስትራክሽን ዲዛይን ድርጅት ሴት ሠራተኞች በሕገ መንግሥቱ በተደነገጉ የሴቶች መብቶች ላይ የግማሽ ቀን ሥልጠና ተሰጠ
March 5, 2020
Show all

በሕገ መንግሥቱ አንቀፅ 40/1 የተደነገገ መብትን ጥሶ የተገኘ መዝገብ ለትርጉም ወደ ፌዴሬሽን ምክር ቤት ተላከ

በሕገ መንግሥቱ አንቀፅ 40/1 የተደነገገ መብትን ጥሶ የተገኘ መዝገብ ለትርጉም ወደ ፌዴሬሽን ምክር ቤት ተላከ

የሕገ መንግሥት ጉዳዮች አጣሪ ጉባዔ የካቲት 18/2012 ባካሄደው መደበኛ ጉባዔ ከመረመራቸው መዝገቦች መካከል አንድ መዝገብ በሕገ መንግሥቱ አንቀፅ 40 ንዑስ አንቀፅ አንድ ላይ “ማንኛውም የኢትዮጵያ ዜጋ የግል ንብረት ባለቤት መሆኑ/ኗ ይከበርለታል/ላታል። ይህ መብት የሕዝብን ጥቅም ለመጠበቅ በሌላ ሁኔታ በሕግ እስካልተወሰነ ድረስ ንብረት የመያዝና በንብረት የመጠቀም ወይም የሌሎችን ዜጎች መብቶች እስካልተቃረነ ድረስ ንብረትን የመሸጥ የማውረስ ወይም በሌላ መንገድ የማስተላለፍ መብቶችን ያካትታል።” በማለት የተደነገገውን መብት ጥሶ የተገኘ በመሆኑ ለመጨረሻ ውሳኔ ወደ ፌዴሬሽን ምክር ቤት እንዲላክ የውሳኔ ሀሳብ አሳልፏል።

ይህ የንብረት ክርክር የሆነው አቤቱታ ለጉባዔው የቀረበው በትግራይ ክልል ነዋሪ ከሆኑ አንድ ግለሰብ ሲሆን፣ አቤቱታ አቅራቢውም ከክልሉ ፍ/ቤት እስከ ፌዴራል ጠቅላይ ፍ/ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት ድረስ ክርክራቸውን ሲያካሂዱ ከቆዩ በኋላ በውሳኔዎቹ ሕገ መንግሥታዊ መብቴ አልተከበረልኝም በማለት ወደ ጉባዔው ያመጡት ነው። ጉባዔውም መዝገቡን ሲመረምር ከቆየ በኋላ በዛሬው ውሎ ከላይ የተጠቀሰውን የሕገ መንግሥት ድንጋጌ የጣሰ ሆኖ ስላገኘው ለውሳኔ ወደ ፌዴሬሽን ምክር ቤት እንዲላክ የውሳኔ ሀሳቡን ሊያሳልፍ ችሏል።

በጉባዔው የዛሬ ውሎ አራት መዝገቦች የተመረመሩ ሲሆን፣ ትርጉም ያስፈልገዋል በማለት የውሳኔ ሃሳብ ካሳለፈበት ጉዳይ ሌላ ሁለት መዝገቦችን ለተጨማሪ ምርመራ በይደር ሲያቆይ አንድ መዝገብ ላይ ደግሞ የሕገ መንግሥት ትርጉም የማያስፈልገው በመሆኑ ውሳኔ በመስጠት ዘግቶታል።